ሱዳን ከኢጋድ አባልነቷ ለቀቀች
ሱዳን፣ ኢጋድ በውስጥ ጉዳዬ ጣልቃ ገብቷል በማለት ከድርጅቱ ጋር ያላትን ግንኙነት ማቋረጧን ዛሬ አስታውቃለች። የሱዳን ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር የኢጋድ የወቅቱ ሊቀመንበር ለሆነችው ጅቡቲ አቻቸው በጻፉት ደብዳቤ፣ ይህንኑ ውሳኔ አሳውቀዋል። ሱዳን ከኢጋድ ጋር ግንኙነቷን ያቋረጠችው፣ በመጭው ሐሙስ ኡጋንዳ ላይ የተጠራው የኢጋድ መሪዎች አስቸኳይ ጉባዔ ወታደራዊውን መንግሥት ሳያማክር የሱዳኑን ጦርነት አጀንዳው ማድረጉንና የፈጥኖ ደራሹን ኃይል እንዲገኙ መጋበዛቸውን በመቃወም ነው። የሱዳኑ ወታደራዊ መሪ ጀኔራል አብዱል ፈታህ አል ቡርሃን በኢጋድ ጉባኤ ላይ እንደማይገኙ ከትናንት ወዲያ ማሳወቃቸው ይታወሳል። ኢጋድ አስቸኳዩን የመሪዎች ጉባኤ የጠራው፣ በሱዳኑ ጦርነት ዙሪያ ለመወያየትና የኢትዮጵያና ሱማሊያ ዲፕሎማሲያዊ ውጥረትን ለማብረድ ነበር።
