ከአብን የለቀቁ አባላት “ንስር” ፓርቲን ሊመሰርቱ እንደሆነ ገለጹ

ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የለቀቁ አባላትን ያሰባሰበ የፖለቲካ ፓርቲ ሊመሰረት እንደሆነ የአደራጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አንተነህ ስለሺ ለአዲስ ጊዜ ገለጹ። ‹‹የአማራ ሕዝብ ንስር ፓርቲ›› በሚል ስም የተደራጀው ይህ አዲስ ፓርቲ ሐሙስ ህዳር 13 ቀን 2016 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ራስ አምባ ሆቴል ምሥረታውን ይፋ እንደሚያደርግ ተነግሮለታል፡፡

ሐምሌ 2 ቀን 2015 ዓ.ም 245 መሥራች አባላት ተሰባስበው በወሰኑት መሠረት ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የዕውቅና ጥያቄ ማቅረቡንና ነሐሴ 11 ቀን 2015 ዓ.ም. ቅድመ ዕውቅና ሰርተፊኬት እንደተሰጠው የፓርቲው አደራጅ ለአዲስ ጊዜ ጨምረው ተናግረዋል፡፡

ከክልል ባለፈ አገር አቀፍ ዕውቅና ለማግኘት እየሠሩ መሆኑንም አያይዘው ገልጸዋል፡፡

የአደራጅ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ አንተነህ ስለሺ የመመሥረቻ ጉባዔ ለማካሄድ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ምርጫ ቦርድ በፈቀደው የሦስት ወራት የመሥራች ጉባዔ ማድረጊያ የዝግጅት ጊዜን በመጠቀም ርዕዮተ ዓለም፣ ፕሮግራም፣ ማኒፌስቶና ድርጅታዊ አሠራርን የተመለከቱ ደንቦችን ጨምሮ የተለያዩ ሰነዶች እየተዘጋጁ መሆናቸውንም አስረድተዋል፡፡

ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ፓርቲ የለቀቁ አባላት በብዛት የሚገኙበት ይህ አዲስ የፖለቲካ ስብስብ ሌሎች አዳዲስ ግለሰቦችንም እንዳካተተ ከአደራጅ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰምተናል።