“በማንኛውም ጊዜ የፀጥታ ችግር ቢከሰት ሃላፊነቱን አልወስድም ” ደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ

15/05/16

በተለያዩ ጊዜያት በፋኖ እና በመንግሥት ታጣቂዎች መካከል ውግያ የተካሄደባት የደብረ ብርሃን ከተማ በአሁኑ ወቅት አንፃራዊ ሰላም በአከባቢዉ ቢስተዋልም ባለው ነባራዊ ሁኔታ አስጊ የሆነ የፀጥታ ችግሮች አሁንም በስጋትነት ያሉ በመሆኑ በማንኛውም ወቅት የፀጥታ ችግር ቢከሰት ሃላፊነቱን እንደማይወስድ የደብረ ብርሃን ዩንቨርስቲ አስታወቀ ፡፡

ነባር ተማሪዎች እና አዳዲስ ተማሪዎች ከጥር 23ቀን 2016ዓ.ም ጀምሮ እንዲገቡ ጥሪ ያደረገው ዩኒቨርስቲው ምንም ዓይነት የፀጥታ ችግር ቢፈጠር ሃላፊነቱን እንደማይወስድ አሳውቋል። የ2016ዓ.ም የመማር የማስተማር ሂደት በአማራ ክልል ባለው የፀጥታ ስጋት ምክንያት የተስተጓጎለ መሆኑን የሚገልጹት የዩኒቨርሲቲው የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ አህመድ ሞሃመድ መስከረም ወር መጨረሻ 2016ዓ.ም የጤና ተማሪዎችን እና የ2016ዓ.ም ተመራቂ ተማሪዎችን እንዲሁም ጥቅምት መጨረሻ የ2015ዓ.ም የመጀመሪያ አመት ተማሪዎች የ2ኛ ሲሚስቴር ትምህርታቸ እንዲቀጥሉ ጥሪ በተደረገላቸው  መሰረት 99 በመቶ የሚሆኑ ተማሪዎችን ተቀብሎ እያስተማረ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ግጭቶች ካሉባቸው ቦታዎች የሚመጡ ተማሪዎች አማራጭ መንገዶች እንዲጠቀሙም ጠይቀዋል፡፡

ከዚህ ቀደም ዩንቨርስቲው ከአዲስ አበባ እና ባቅራቢያው ካሉ አካባቢዎች ለሚመጡ ለአዳዲስ ተማሪዎች መጓጓዣ ያዘጋጅ የነበረ ቢሆን በዚህኛው አመት ለሚገቡ ተማሪዎች ግን ይህን ማድረግ አንዳልተቻለ አቶ አህመድ አክለዋል።

ደብረብርሐን ከተማ ታሕሳስ 24 ቀን 2016 ዓም በፋኖ ታጣቂዎች እና በመንግሥት የፀጥታ ሃይሎች መካከል በተፈጠረ ግጭት በርካታ ሰዎች ለሞት መዳረጋቸው ይታወሳል።