14/05/2016
ፕሬዝዳንት ሞሃመድ ወደ ዶሃ የተጓዙት፣ በቅርብ ጊዜያት በሱማሊያ በተፈጠሩ እንዳንድ ክስተቶች ዙሪያ ከአገሪቱ መሪዎች ጋር ለመወያየት እንደኾነ የፕሬዝዳንቱ ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። ኢትዮጵያ ከሶማሊላንድ ጋር በተፈራረመችው የባሕር በር የመግባቢያ ስምምነት ሳቢያ በሱማሊያና ኢትዮጵያ መካከል ውጥረት ከተፈጠረ ወዲህ፣ ፕሬዝዳንት ሞሃመድ በኤርትራና ግብጽ ይፋዊ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል።
ሶማሊላንድ ግን ከኢትዮጵያ ጋር ከተፈራረመችው የባሕር በር የመግባቢያ ስምምነት ጋር በተያያዘ ማናቸውንም የውጭ ጣልቃ ገብነት እንደምትቃወም አስታውቃለች። ሶማሊላንድ በውጭ ጉዳይ ሚንስቴሯ በኩል ትናንት ባወጣችው መግለጫ፣ ግብጽ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቷን እንደ ሱዳን፣ ሊቢያና ጋዛ በመሳሰሉ ግጭቶች ባሉባቸው ጎረቤቶቿ ላይ ብታውለው ይሻላታል ብላለች። ቀጠናዊ ጉዳዮችን በንግግርና ትብብር ለመፍታት ቁርጠኛ መሆኗን የጠቀሰችው ሶማሊላንድ፣ በቀጠናው ሰላምና ልማት ለማምጣት ከሁሉም አገራት ጋር ዲፕሎማሲያዊ ውይይቶችንና ትብብሮችን እንደምታደርግ ገልጣለች።
