በኢትዮጵያ የሚገኙ ስደተኞች ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው መኖር የሚችሉበት የቃል ኪዳን ሰነድ መዘጋጀቱ ተገለጸ

ሐሙስ ጥቅምት 15 ቀን 2016

በኢትዮጵያ የሚገኙ ስደተኞች ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው መኖር የሚችሉበት የቃል ኪዳን ሰነድ መዘጋጀቱን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ገልጸዋል።

በስዊዘርላንድ ጀኔቭ በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የስደተኞች ጉባኤ ላይ ኢትዮጵያ የምታቀርበውን ስድስት አዲስ የቃል ኪዳን ሰነድ ለማጽደቅ የተዘጋጀ የከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው።

በመድረኩ ላይ የተገኙት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፤ ኢትዮጵያ አሁን ላይ ከተለያዩ አገራት የመጡ ከ1 ሚሊዮን በላይ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ ላይ ትገኛለች ብለዋል።

በኢትዮጵያ የሚገኙ ስደተኞችም ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው መኖር የሚችሉበት የቃል ኪዳን ሰነድ መዘጋጀቱን ገልጸዋል።

እኤአ በ2019 በተካሄደው ዓለም አቀፍ የስደተኞች ጉባኤ ላይ አራት ቃል ኪዳኖችን በትምህርት፣ በቴክኒክና ሙያ ስልጠና፣ በማዕድንና መሰል ዘርፎች በማቅረብ ውጤታማ ስራ ማከናወኗንም አስታውሰዋል።

በአራቱ ቃል ኪዳኖች ያስመዘገበችውን ስኬት በቀጣይ ታህሳስ ወር በሚቀርቡት ስድስት ቃል ኪዳኖች መድገም የሚያስችል እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኑን ገልጸዋል።

በመሆኑም በታህሳስ 2023 በስዊዘርላንድ ጀኔቭ በሚካሄደው የዓለም የስደተኞች ጉባኤ ላይ ኢትዮጵያ የምታቀርበው አዲስ ቃል ኪዳን በኢትዮጵያ የሚገኙ ስደተኞች ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው መኖር የሚችሉበት ነው ብለዋል።

ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብሎ በማስተናገድ ያላት ሚና የጎላ መሆኑን ኹሉም ሊገነዘብ ይገባል ሲሉም ተናግረዋል።

የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ጠይባ ሀሰን፤ ኢትዮጵያ በ26 የመጠለያ ጣቢያዎች ከ1 ሚሊዮን በላይ ስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎችን ተቀብላ እያስተናገደች መሆኑን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የስደተኞች መብትና ጥበቃን ማስከበር የሚያስችል ተራማጅ የሕግ ማዕቀፍ አዘጋጅታ ስደተኞችን እያስተናገደች መሆኑንም አብራርተዋል።

የስደተኞች ጉዳይ ዓለም አቀፋዊ ይዘት ያለው በመሆኑ ቀጣናዊ፣ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ትብብር መፍጠር ይገባል ነው ያሉት።

በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር የኢትዮጵያ ተወካይ አንድሪው ምቦጎሪ በኢትዮጵያ ያለውን የስደተኞች አያያዝ በቅርበት እንደሚከታተሉ እና እገዛ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆናቸውን ማረጋገጣቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

የኢጋድ የጤናና ማህበራዊ ልማት ዳይሬክተር ማዳም ፈቲያ አልዋን በበኩላቸው፤ ኢጋድ በኢትዮጵያ የሚከናወነውን የስደተኞች አያያዝ ለመደገፍ ፈጣን የተግባር እርምጃ ይወስዳል ብለዋል።